የባንክ ቀሪ ዕዳ ማወራረጃ የሕይወት ዋስትና ከባንክ ገንዘብ ተበድረው የመኖሪያ ቤት ለሚሰሩ የሚሰጥ ሲሆን ዋስትና የተገባለት ቤት ባለቤት ከባንክ የተበደሩትን ዕዳ አጠናቀው ሳይከፍሉ ከዚህ ዓለም በሞት በሚለዩበት ወቅት ቤተሰብ ዕዳ በመክፈል ወይም ቤቱ ተሸጦ ለዕዳ ተከፋይ እንዳይሆን ቤተሰብና ልጆች ያለመጠጊያ እንዳይቀሩ የሚያደርግ መጠለያ የሚሰጥ ዋስትና ነው፡፡ የባንክ ቀሪ ዕዳ ማወራረጃ የሕይወት ዋስትና አንድ ተበዳሪ ከባንኩ ለሚበደረው ገንዘብ ለሕይወት ዋስትና የሚገባ ሲሆን የባንኩ ተበዳሪ ወይም ተበዳሪዎች ለባንኩ መክፈል የሚገባቸውን የብድር ገንዘብ ከፍለው ከማጠናቀቃቸው በፊት ከዚህ ዓለም በሞት ከተለዩ በብድሩ ውል መሠረት ቀሪ ዕዳውን የኢትዮጵያ መድን ድርጅት ሟችን በመተካት ለባንኩ ክፍያውን ይፈፅማል፡፡
የባንክ ቀሪ ዕዳ ማወራረጃ ዋስትና ተጠቃሚ ለመሆን፡- 1. ተበዳሪው የመድን መግቢያ ማመልከቻ ቅፅ መሙላት፣ 2. በብድሩ መጠን ላይ በመመስረት አስፈላጊ ሲሆን በድርጅቱ ክሊኒክ ወይም ከአዲስ አበባ ውጪ ከሆነ ከግል ክሊኒክ ወይም ሆስፒታል የጤና ምርመራ ማቅረብ፣ 3. ለዋስትናው የሚከፈለውን የረጅም ጊዜ አረቦን በአንድ ጊዜ መክፈል ያስፈልጋል፡፡ ይህን የባንክ ቀሪ ዕዳ ማወራረጃ የሕይወት ዋስትና በጣምራ ከባለቤት ጋር ባልና ሚስት በመሆን ለመግዛት ይቻላል፡፡ ቀሪው ዕዳ ከመጠናቀቁ በፊት ከሁለት አንዳቸው ከዚህ ዓለም በሞት ከተለዩ ቀሪውን ዕዳ የኢትዮጵያ መድን ድርጅት ለባንክ ይከፍላል፡፡
|